ሀሳቤ መች አስቦልኝ ፣ እዚህ አድርሶኝ ማወቄ መች ቁጥር ይገባና ፣ ድል ያረኩት ተጠንቅቄ ከንቱ መሆኑ ጭንቀቴ… — Mihret Zenebe (mercy) — TG.ME

ሀሳቤ መች አስቦልኝ ፣ እዚህ አድርሶኝ ማወቄ
መች ቁጥር ይገባና ፣ ድል ያረኩት ተጠንቅቄ
ከንቱ መሆኑ ጭንቀቴ ፣ ማወቁ መቼ ተሳነኝ
ሰውነት ቢይዘኝ እንጂ
ከእምነቴ ሀይል በላይ ፣ ገሀድ ህይወቴ ቢጫነኝ ።

"ያልፋል" አትብለኝ አልፋለሁ
ልክ ነው ይረሳል ረግፋለሁ
እውቀቴ አድማስ ፣ቢሻገር ብሰማም  ሲባል ብዙ
ሰማይ ከመሬት ሲላቀቅ ፣ ይጀምረኛል መቅበዝበዙ።

"ያልፋል "ማለት አያለፋም
ትናንትና ምን ቢዘምም ፣ ከዛሬ  ጽልመት አይከፋም
ልክነትህን ልቀበል ፣ ካለመቻሌ ተስማማ
ድንግዝግዝታዬ ይዋጥልህ ፣ ዳግም ተስፋን እንድጫማ ።

ሀሳብን ሽቼ አይደለም ፣  ምክርን ውስጤ ናፍቆ
የሚናገርን አንደበት ፣ ምክንያት ከውጤት አራቆ
"ከብደኝ ፣ደከመኝ" ስልህ  ፣" ለምን ?" እንዳይሆን መልስህ
ይልቅ ዝም በልና ፣ አጥር ሁንልኝ በክንድህ።

ሳትደርስብኝ ልትደርስልኝ  አትታገል
መች ተችሎት ፣ ተግሳጽ ሁሉን መገላገል ።

" ከበደኝ ፣ ደከመኝ " ስልህ ፣ "እንዴት?" እንዳይሆን ምላሽህ
ትከሻዬ እና ቀንበሬን ፣ አታወዳድረው  ከራስህ
ባለፋከው ነገር ሚዛን ፣ አይነውረብህ ሽንፈቴ
የእኔ አቅም እዚህ ድረስ ነው ፣ "ልክ ነሽ " በለኝ በሞቴ ።
         
                              ምሕረት ዘነበ
❤5🔥2😢1
August 1, 2026 132