Diinii kee Anaakara (Md Ali): post #4677 — TG.ME

የማለዳ መልእክት (46)
~
ታላቁ ሶሓቢይ ሰዕድ ብኑ አቢ ወቃስ (ረዲየላሁ ዐንሁ) ባስተላለፉት ሐዲሥ የአላህ መልእክተኛ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም እንዲህ ብለዋል፦

إن الله يحب العبد التقي الغني الخفي
"አላህ፡ አላህን ፈሪውን፣ በራሱ የተብቃቃውን እና ድብቁን (ዝናን የማይፈልገውን) ባሪያውን ይወዳል።"

ኢማሙ ሙስሊም በሶሒሓቸው ውስጥ ዘግበውታል። [ሶሒሕ ሙስሊም፡ 2965]

=

ዑለማኦች የአላህን ውዴታ የሚያስገኙትን እነዚህን ሦስት ባሕርያት እንደሚከተለው አብራርተዋቸዋል፦

1. «አል-ተቂይ» (ፈሪሃ-አላህ ያለው / አላህን ፈሪ):-

ይህ ባሪያ የአላህን ትዕዛዛት በመፈጸም እና ክልከላዎቹን በመራቅ የአላህን ትእዛዝ የሚጠብቅ፣ በአላህ ትዕዛዝና ኃጢአትን እንዲሁም አጠራጣሪ ነገሮችን በመራቅ በእርሱ እና በአላህ ቅጣት መካከል ከልላይን የሚያደርግ ነው።

2. «አል-ገኒይ» (ሀብታም / የተብቃቃ):-

«ሀብት/መብቃቃት» በሚለው ትርጉም ላይ በሁለት አቅጣጫ ገልጸውታል፦

* የነፍስና የቀልብ መብቃቃት (ይህ ይበልጥ ጎላ ያለና ተመራጩ ትርጉም ነው)፦

ባሪያው አላህ በወሰነለት እና በሰጠው ሲሳይ የሚረካ፣ በሰዎች እጅ ካለው ነገር ተብቃቅቶ በአላህ ብቻ የሚብቃቃ፣ ቀልቡ በኢማን እና በየቂን (እርግጠኝነት) የሞላ መሆን ነው። ነቢዩም ﷺ፦ «ولكن الغنى غنى النفس» («እውነተኛ ሀብት ማለት ግን የነፍስ (የቀልብ) መብቃቃት ነው») ብለዋል።

* የገንዘብ ሀብት፦

ይህም ሀብቱን በበጎ አድራጎት፣ በመልካም ሥራዎች እና ሰዎችን በመጥቀም ላይ የሚያውል፣ ሀብቱ ከአላህ እገዛ እንዳይዘናጋው የአላህን ሐቅ እየፈጸመ የሚያመሰግን ሀብታም ነው።

3. «አል-ኸፊይ» (ድብቁ / ራሱን የማያገዝፈው):-

* ዝናን፣ ሥልጣንን እና በምድር ላይ ከፍ ማለትን የማይሻ፣ ይልቁንም ጌታውን በመገዛት፣ የራሱን ጉድለቶች በመመልከት እና ራሱን በማረም ላይ ብቻ የተጠመደ ሰው ማለት ነው።

* በተጨማሪም፦ ፍጹም ለአላህ ብቻ ብሎ ለመስራት (ኢኽላስ) እና ይዩልኝ ስሙልኝን (ሪያእ) በመፍራት መልካም ሥራዎቹንና አምልኮቶቹን (እንደ ድብቅ ሶደቃና የሌሊት ሶላት ያሉትን) ሰው እንዳያይበት የሚደብቅ ሰውም በዚህ ውስጥ ይካተታል።

||
(ኢብኑ ሙነወር፣ ረቢዑል አወል 04/1448)
=
የቴሌግራም ቻናል፦
https://t.me/IbnuMunewor
https://t.me/IbnuMunewor
Telegram
Ibnu Munewor (ኢብኑ ሙነወር)
كناشة ابن منور
August 17, 2026 141