ከኤሌክትሪክ ኃይል ኤክስፖርትና ተያያዥ አገልግሎቶች 474 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ተገኘ
++++++++++++++++++
#ጋዜጣ_ፕላስ- ኢትዮጵያ በተጠናቀቀው 2018 በጀት ዓመት ከኤሌክትሪክ ኃይል ኤክስፖርት፣ ከሀገር ውስጥ ዳታ ማይኒንግና ከቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ሽያጭ 474 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ገቢ ማግኘቷን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አስታወቀ።
የተቋሙ የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ሞገስ መኮንን ለጋዜጣ ፕላስ እንዳስታወቁት፣ ከተገኘው አጠቃላይ ገቢ 120 ሚሊዮን ዶላር ገደማ የሚሆነው በቀጥታ ለጎረቤት ሀገራት ከተደረገ የኤሌክትሪክ ኃይል ሽያጭ የተገኘ ነው። ቀሪው በሀገር ውስጥ ሆነው የውጭ ምንዛሬ ከሚከፍሉ የዳታ ማይኒንግና የቴክኖሎጂ ተቋማት የተሰበሰበ ነው ብለዋል።
ኢትዮጵያ በምሥራቅ አፍሪካ ቀጣና የኤሌክትሪክ ኃይል ትስስርን ለማጠናከር በሚደረገው ጥረት ውስጥ ዋና ተዋናይ ሆና እያገለገለች መሆኗን ያነሱት አቶ ሞገስ፤ በአሁኑ ወቅት ወደ ጅቡቲና ኬንያ የሚደረገው የኃይል ኤክስፖርት በተሳካ ሁኔታ እየቀጠለ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በተለይም ከኬንያ ጋር ያለው የኃይል ትስስር አፈጻጸም ከፍተኛ ውጤት እየታየበት እንደሚገኝም ጠቅሰዋል።
በሁለቱ ሀገራት ስምምነት መሠረት በከፍተኛ የኃይል ፍላጎት ሰዓታት እስከ 200 ሜጋ ዋት እንዲሁም በዝቅተኛ የፍላጎት ሰዓታት ደግሞ 65 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል እየቀረበ ይገኛል። የኃይል አቅርቦቱ የኬንያን የኤሌክትሪክ ሲስተም መረጋጋት ከማስጠበቅ ባሻገር፣ ሀገሪቱ ከውጭ ከምታስገባው ኢነርጂ እስከ 90 ከመቶ የሚሆነውን ከኢትዮጵያ እንድታገኝ አስችሏታል።
በሌላ በኩል፣ ወደ ሱዳን ይደረግ የነበረው የኃይል ኤክስፖርት ሀገሪቱ በገባችበት የእርስ በእርስ ግጭት ምክንያት ሙሉ በሙሉ የተቋረጠ ሲሆን፤ በጦርነቱ ምክንያት በሱዳን በኩል ያለው የኢነርጂ ተሸካሚና አስተላላፊ መሠረተ ልማቶች በከፍተኛ ሁኔታ በመጎዳታቸው የኃይል አቅርቦቱ ሊቆም ችሏል።
ከሱዳን ጋር የተፈጠረው የኃይል መቋረጥ ከመሠረተ ልማት ጋር ብቻ የተያያዘ እንጂ ከቀደመ ክፍያ ወይም ከውዝፍ ዕዳ ጋር የሚገናኝ አለመሆኑን አስታውቀዋል።
የሀገር ውስጥ የኃይል ማመንጨት አቅምን በተመለከተ፣ የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ከተያዘለት እቅድ ውስጥ 99 ነጥብ አምስት ከመቶ ያህሉን በማሳካት ከፍተኛ አፈጻጸም ማስመዝገቡ ተጠቁሟል። ሀገሪቱ ካመነጨችው አጠቃላይ 35 ቴራ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል ውስጥ 51 ነጥብ አምስት ከመቶውን ወይም ከግማሽ በላይ የሚሆነው የተመረተው ከሕዳሴው ግድብ መሆኑንም አቶ ሞገስ ተናግረዋል።
የኤሌክትሪክ ኃይል ኤክስፖርት ከውጭ ምንዛሬ ግኝት ባሻገር፣ ከጎረቤት ሀገራት ጋር በሰጥቶ መቀበል መርኅ ላይ የተመሠረተ የኢኮኖሚና የሰላም ትስስር ለመፍጠር ትልቅ ሚና እየተጫወተ ይገኛል።
የአፍሪካ ኅብረት የ“አጀንዳ 2063” አካል የሆነውን የፋሲሊቲዎችና የመሠረተ ልማት ትስስር ግብ ለማሳካት ኢትዮጵያ የበኩሏን ድርሻ እየተወጣች መሆኗን ያነሱት ዳይሬክተሩ፤ ኢትዮጵያ ከኃይል ሽያጭ የምታገኘው የውጭ ምንዛሬ በሀገር ውስጥ ያለውን የኤሌክትሪክ ተደራሽነት አሁን ካለበት 54 ከመቶ ለማሳደግና አዳዲስ የመሠረተ ልማት ፕሮጀክቶችን ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ውስጥ ከፍተኛ እገዛ እንደሚያደርግም ገልጸዋል።
በዮርዳኖስ ፍቅሩ
7August 19, 2026 4.2K 4