ባለትዳር ሴት አባለግኩ፤ "አወጣሻለሁ" አልኳት። እንደተናገርኩት አደረግኩ።
እንዳሸነፍኳት ተሰምቶኝ ነበር። ከቤቴ ወጥታ በሩን ስትዘጋ የድሉ ድምፅ አብሮ ጠፋ።
ለጥቂት ቆሜ ቀረሁ። በቤቱ ውስጥ የሽቶ መዓዛ ትታ ሄዳለች።
አልጋው ላይ የተጨማደደውን ሸሚዜን አየሁ፤ ወለሉ ላይ የፀጉሯ አንድ ዘለላ ወድቋል።
አሸንፌያታለሁ።
ድሉ ደስ ሊያሰኝ ይገባ ነበር። ነገር ግን ውስጤ ባዶ ሆነ
መስታወቱ ፊት ቆምኩ።
መስታወቱን እያየሁ አባቴን አሰብኩ።
አባቴ እናቴ ከከዳችው በኋላ ሌላ ሰው ሆነ፤ አዘውትሮ መስታወት ይመለከት ጀመረ።
እናቴ ክፉ ናት!... ከአባቴ ጓደኛጋ አንሶላ በመጋፈፍ አባቴን ሰበረችው!
... ቤታችን በአንድ ቀን አልፈረሰም። በቀስታ ዘመመ፣ በዝግታ ወደቀ። ቤታችን ፈረሰ፣ የአባቴ አለም ተገንዶሶ ወደቀ።
መጀመሪያ የአባቴ ሳቅ ጠፋ። ከዚያ ድምፁ ሰለለ ፣ መናገር ጠላ። የፊቱ መስመሮች በዙ ፣ ከአይኑ በታች ጠቆረ ፣ ጉንጩ ጎረጎደ።ከንፈሩ ተሰነጠቀ።
እናቴ አባቴን በቁም ገደለችው።
ተጫዋችነቱ ከስሞ ሃዘንተኛ ሆነ ፣ አረቄና ሲጃራ መሸሸጊያው ሆኑ።
አንድ ምሽት በመስታወት ፊት ቆሞ አየሁት። ፀጉሩን እየዳሰሰ ነበር። ፊቱን ከግራ ወደ ቀኝ ይነቀንቃል። ዓይኖቹን ስር ሃዘን ተፅፏል።
"አባ?"
ደነገጠ። የገዛ ልጁ ድምጽ አስደነገጠው። ፈገግ ለማለት ሞከረ። ፈገግታወሰ ሙት ነው።
መስታወት ፊት ሲቆም በድብቅ ማየት ጀመርኩ። መስታወት ፊት ቆሞ "ከእኔ ምን አጣች? ምን ጎደለብኝ?" እያለ ራሱን ይጠይቃል።
እናቴን አልጠላኋትም። እናቴን አለመጥላቴ ይበልጥ አስከፊ ነበር።
እናቴን እወዳታለሁ ፤ እየወደድኳት አፍርባታለሁ።
ሰዎች በሹክሹክታ ያሟታል። "አመንዝራ" ይሏታል። ለአባቴ ከንፈር ይመጡለታል።
ሰዎች ሲያዩኝ "ምናልባት ከሌላ ወንድ ይሆናል የወለደችው" ይሉኛል። "ወፍ ዘራሽ ዲቃላ" ይሉኛል።
የእናቴ የሃጢያት ቀንበር ነፍሴን አጉብጧል።
ለራሴ ቃል ገባሁ። "እንደ አባቴ አልሆንም" አልኩ። ሴት ልጅ በገዛ ፍቃዷ እንድትተወኝ ላለመፍቀድ ማልኩ።
በሌላ ወንድ የምተካ መሆን የለብኝም። ራሴን በማንም እጅ አላስቀምጥም።
ከባለትዳር ሴት ጋር ተኛሁ። ሆነ ብዬ አባለግኳት።
ለመጀመሪያ ጊዜ ያየኋት ቀን ያስተዋልኩት ውበቷን አልነበረም። ቀለበቷን እንጂ!
የግራ እጇን ስታንቀሳቅስ የፀሐይ ብርሃን በቀለበቷ ላይ ይጫወት ነበር። ቀለበቷን ትነካካለች።
ሳልጠይቃት “ባለትዳር ነኝ” አለችኝ። ባል ስላላት ብቻ ልተኛት ፈለግኩ። ተኝቼ ድል ላደርጋት...
"አወጣሻለሁ" አልኳት
"ባል አለኝ" አለች
“አውቃለሁ”
ዓይኖቿ ጠበቡ።
"እንዲህ የምታየኝ ለምንድነው?"
"ራቁትሽን ምን እንደምትመስዪ እያሰብኩ"
ፊቷ ላይ የነበረውን ቁጣ አልረሳውም። ተደፈርኩኝ አለች። ተናቅኩኝ አለች።
እናቴ አባቴ ላይ ስትወሰልት ባለትዳር ነበረች።
የቀለበት ብርሃን ቤትን ከመፍረስ የሚያድን ቢሆን፣ የእኛ ቤት አይፈርስም ነበር።
“ፈተና ነህ” አለችኝ።
... ተቀራረብን። ምክንያት ፈጥራ ወደ እኔ መጣች፤ ሰበብ ፈጥሬ በሬን ከፈትኩላት።
አልጋዬ ላይ እርቃኗን ተኝታ የአባቴን ስብራት አሰብኩ፤ የአባቴን ውርደት እያሰብኩ ጋለብኳት።
ትላንት ከባሏ ሰርቄ ተኛኋት።
ዛሬም ደወልኩላት
“ነይ” አልኳት። እየጠራኋት ሳይሆን እያዘዝኳት ነበር።
“ለምን?”
ምን ልበላት ነበር?
እንደገና ምረጪኝ?
የምተው እንዳልሆንኩ አሳዪኝ?
አባቴን እንዳልሆንኩ አረጋግጪልኝ?
“ለወሲብ።” አልኳት
የማደርገውን እያሰብኩ ራሴን ጠላሁ። ድምጼ ለእርሷ የጌታ ሊመስላት ይችላል። እውነቱ ግን እንዳትመጣ የሚፈራ ሰው ድምፅ ነበር።
“እሺ” አለች።
እንድትመጣ የፈለግሁት ሰውነቷን ስለፈለግሁ ብቻ አልነበረም። ዳግመኛ እንድትመርጠኝ ፈልጌ ነበር። የምርጫዋ ባለቤት እኔ ነኝ ብዬ ለራሴ ማሳመን ፈልጌ ነበር።
ሠላሳ ደቂቃ አለፈ።
መጣች።
ባሏን አሰብኩ። በባሏ ውስጥ አባቴን አየሁት። ሚስቱን እየጠበቀ ያለው ሰው ታየኝ።
አባቴም እንደዚያ ነበር?
እናቴን ለመቅጣት እየሞከርኩ ነበር። የእናቴን ዓይነት ሴቶች በማሸነፍ ከአባቴ የተሻለ ሰው እሆናለሁ ብዬ አምኜ ነበር።
...ከአባቴ የተለየ አልሆንኩም።
አባቴ በሌላ ወንድ ተተክቶ ራሱን አጣ። እኔ ደግሞ ሌላ ወንድ የአባቴን ውድቀት እንዲወድቅ አደረግኹ።
...ወደ ውስጥ ገባች።
አባቴ ታወሰኝ፤ በመስታወት ፊት ቆሞ ራሱን የሚጠይቀው አባቴ።
ምን አጎደልኩባት? የሚለው አባቴ
ከአባቴ ምን ተሻልኩ?
"ተመለሺ" አልኳት። ድንገት አይኗ እንባ አረገዙ
"ምን አጠፋሁ?"
"ተመለሺ!"
አለቀሰች።
በሩን ዘጋሁባት።
ሕይወቴን ሙሉ ካለፈ ጦርነት ጋር እየተዋጋሁ ነበር።
ያንን ጦርነት ለማሸነፍ ስሞክር፣ ሌላ ሰው እንደ አባቴ እንዲሰበር አደረግኩ።
Via ተስፋአብ ተሾመ