በመዲናዋ ብቃታቸው የተረጋገጠ ከ4 መቶ በላይ ስፔሻላይዝድ የጥርስ ህክምና ተቋማት መኖራቸው ተገለፀ
የአዲስ አበባ ምግብና መድኃኒት ባለስልጣን በከተማዋ 4መቶ2 ብቃታቸው የተረጋገጠ ስፔሻላይዝድ የጥርስ ህክምና ተቋማት መኖራቸውን አስታውቋል።
ባለስልጣኑ የሚቆጣጠራቸውን እነዚህን ተቋማት እውቅና ለመስጠት መዘጋጀቱንም ገልጿል።
ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ከሮቫ ኤቨንትስ እና መልቲሚዲያ ጋር በመተባበር በጥርስ ሕክምና አገልግሎት አሰጣጥ የላቀ ሥራ ላከናወኑ የጥርስ ሕክምና ተቋማትና ባለሙያዎች ያዘጋጀውን የእውቅና እና የሽልማት መድረክ ይፋ አድርጓል።
ፕሮግራሙ በታካሚ እንክብካቤ፣ በክሊኒካዊ ብቃት፣ በንጽህና እና በማህበረሰብ ላይ አዎንታዊ ተፅዕኖ በማሳደር ረገድ የላቀ አፈጻጸም ያስመዘገቡ ተቋማትን እውቅና መስጠትን ግብ ያደረገ ነው።
ፕሮግራሙ እውቅና ከመስጠት ባለፈ ሰፊ ሀገራዊ ፋይዳ እንዳለው
ተነስቷል።
የአዲስ አበባ ምግብና መድኃኒት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ሙሉእመቤት ታደሰ፥ የዕውቅናው አላማ በአዲስ አበባ ዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቁ የጥርስ ሕክምና ማዕከላት እንዲስፋፉ ማድረግ እንደሆነ አንስተዋል።
15 የዕውቅና መስፈርቶች መኖራቸው የተገለፀ ሲሆን፥ ተቋማቱ ከአንድ በላይ በሆኑ መስፈርቶች መወዳደር እንደሚችሉ ተነስቷል።
ለዚህ ሲባል የተዘጋጀ ዌብሳይት መኖሩም ተገልጿል።
የዕውቅና ሽልማቱ 70 በመቶ በባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ግምገማ እና 30 በመቶ በህዝብ ድምፅ እና ምርጫ የሚደረግ ይሆናል።
በየዓመቱ ደረጃውን እና ፕሮፌሽናሊዝምን በጠበቀ መልኩ የሚከናወን መርሀ ግብር እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል።
ሽልማቱ በጥቅምት 2019 የሚካሄድ መሆኑም ተገልጿል።
እስከዳር ግርማ
ነሐሴ 26/2018 ዓ.ም
September 1, 2026 1.1K 7