“ዮም ፍሥሐ ኮነ በእንተ ልደታ ለማርያም፤ በማርያም ልደት ምክንያት ዛሬ ደስታ ሆነ!” (ቅዱስ ያሬድ)
ቅድስት ሐና እና ቅዱስ ኢያቄም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በአድባረ ሊባኖስ ግንቦት አንድ ቀን ወለዷት፡፡ በዚያን ጊዜ ጠላታቸውን ለመሸሽ በስደት ላይ ስለነበሩ ምግብ አልያዙም፤ ስንቃቸውም ‹‹ንፍሮና ጥራጥሬ›› ነበር፡፡ በዚህም የእመቤታችን ማርያምን የልደት በዓል በሕዝበ ክርስቲያን ዘንድ ንፍሮ እየተበላ ይከበራል፡፡ የነቢያቱ ትንቢት የተፈፀመበት፣ የብሉይ ኪዳን ማብቂያ የሐዲስ ኪዳን መጀመሪያ ናትና ልደቷ ለሰው ልጆች ሁሉ (ለሕያዋን ሁሉ) ታላቅ የደስታ ቀን ነው፡፡
በንጽህናዋ እና በቅድስናዋ ተደንቀው ሰማያውያን ቅዱሳን መላእክትም ያመሰግኗታል፡፡ ቤተ ክርስቲያን የቅድስት ድንግል ማርያምን ልደት በታላቅ ድምቀት የምታከብረው ከዚህ ታላቅ በዓል በረከት ረድኤትን እንድናገኝበት ነው፡፡ የክርስቶስ እናት ዛሬ ተወልዳለችና፤ በሥርዓት ቤተ ክርስቲያን መሰረት በቀናች በተዋሕዶ እምነት ሆነን፤ የድኅነታችን ምክንያት የሆነችውን ድንግል ማርያምንም እያመሰገንን ልናከብረው ይገባል፡፡
በመጻሕፍት አምላካውያት (አሥራው መጻሕፍት) እና በሊቃውንት አበው አስተምህሮ የተነገሩ የእመቤታችንን ቅድስት ድንግል ማርያም ንጽሕናዋን ቅድስናዋን የሚመሰክሩ መውድሳት ቅኔያትና ዝማሬያት እንዲሁም በሰፊው የተገለጡትን ምስክርነቶች ስንመለከት እንዲሁ እንደ እንግዳ ደራሽ የተገኙ እንዳልሆነ አስተዋይ ሰው በቅጥነተ ሕሊና ቢረዳው የሚያውቀው እውነት ነው፡፡
ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ሲነሳ፣ በተለይም እመቤታችንን ማመስገን ማለት እርሷን እንደ ፈጣሪ መመልከት፤ ከዚያም ባለፈ እንደ አምልኮ ባዕድ አድርገው የሚመለከቱት እና ያልታደሉ የዘመኑ እንክርዳዶች እና አረሞች፣ ጸላዔ ሠናያት በከንቱ ትጋት የሚያገለግሉ መናፍቃን ቁጥራቸው ከጊዜ ወደጊዜ መብዛት በተጣመመ የሐሰት ትምህርታቸው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የምትመሰገንበትን ምስጋና መቃወም ዛሬ የተጀመረ ሳይሆን ቀድሞም የነበረ ነው፡፡
ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለእመቤታችን ድንግል ማርያም የምታቀርበው ምስጋና የመቃወም ነገር መሠረቱ ምንድን ነው? ስንል የመጀመሪያው በክህደት እና በኑፋቄ ትምህርት መወሰድ ሁለተኛ ደግሞ የተስተካከሉ እና እንከን የሌለውን የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ባለመረዳት እና በስሜት መነዳት (መመራት) መሆኑን የምንመለከተው ነው፡፡
በኦርቶዶክሳዊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጥላ ሥር ለተሰበሰቡ ክቡራን ምእመናን የቤተ ክርስቲያናቸውን አስተምህሮ በአግባቡ ከርቱዓን መምህራን እና በቅዱሳት መጻሕፍት አማካኝነት ማወቁ፤ በተለይ በዘመናችን ለሚዘራው የክህደት አስተምህሮ እንደ ጽድቅ ጋሻ ሆኖ የሚያገለግል ነው፡፡
በተለይ ስለ ወላዲተ አምላክ ድንግል ማርያም ስለሚሰጣት ክብር እና ሞገስ ማወቅ ማለፊያ ነው፡፡ በዚህም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ለማመስገን የሚያስፈልግ መሠረታዊ ነገር ምንድን ነው? ለመሆኑ ሰው እንዲሁ ከመሬት ተነስቶ ለእመቤታችን ምስጋና እና ክብር መስጠት ይችላልን? እመቤታችንን አለማመስገን እና አለማክበርስ ውጤቱ ምንድን ነው የሚለውን በአጭሩ እንደሚከተለው እንመለከታለን፡፡
ይቀጥላል . . .
@Eotc_Books_By_Pdf
@Eotc_Books_By_Pdf







